በኦርቶዶክሳዊት ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ባህልና ትውፊት እና ሥርአት መሰረት ዐቢይ ጾም ከሰባቱ አጽዋማት አንዱና ዋነኛው፤ጌታ ከተጠመቀ በኋላ የጾመው የአርባ ቀን ጾም ነው፡፡ምእመናን ጌታቸው ያደርገውን ምሳሌ ተከትለው ይጾሙታል
1.
ዐብይ ጾም ይባላል፡፡
ሌሎች አጽዋማት ከቅዱሳን አበው የወረስናቸው የኑሮአቸው ፍሬዎች (ዕብ13፡-7)
ሲሆኑ ይሄኛው ግን በጌታችን በመዳኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ የተመሰረተ በመሆኑ ዐቢይ (ታላቅ)
ይባላል፡፡
የጌታ ጾም ስለሆነ ታላላቅ ፈተናዎች (አርስተ ሃጣውእ)
ድል የተነሱበት ድል የሚነሱበት ጾም ስለሆነም ዐቢይ ጾም ይባላል፡፡
2.
ጾመ ኁዳዴ ይባላል፡፡
ሁዳድ ማለት የመንግስት ርስት ማለት ነው፡፡ የመንግስት ሁዳድ በሚታረስበት ጊዜ አዝመራው በሚሰበሰበት ጊዜ ልጅ ዐዋቂ ሳይባል የመንግስት ዜጋ ሁሉ ለሥራ ታጥቆ እንደሚነሳ ይህንንም ጌታ ጾም የጌታ ወይም የጌታ ሁዳድ የክርስቶስ ዜጎች የሆኑ ምእመናን ሁሉ ይጾሙታልና ጾመ ሁዳዴ ይባላል፡፡
3.
የካሳ ጾም ይባላል፡፡
አባታችን አዳምና እናታችን ሔዋን ከገነት የተባረሩት ለውርደት ሞትና ለሲዖል ባርነት የበቁት በመብል ምክንያት ነበር፡፡ በሆዳምነቱ የወደቀውን የሰው ልጅ በፈቃዱ በጾመው ጾም ካሠው እንዲሁም አዳም ከገነት ሲባረር ረሃበ ጸጋ (መንፈሳዊ ረሃብ) ደርሶበት ነበርና ረሃቡን በረሃብ ካሰለት፡፡ የእኛን ረሃብ እርሱ ተራበ፡፡
4.
የድል ጾም ይባላል፡፡
ጌታችን ተጠምቆ እለቱን ወደ ገዳመ ቆሮንጦስ በመሄድ ከሰው ተለይቶ አርባ መአልትና
አርባ ለሊት በመጾም አዳምና ሔዋንን በመብል የረታቸውን ዲያብሎስ እርሱ ድል አደረገላቸው፡፡ዲያብሎስን ድል ያደርግ ዘነድ ከዚህ
ዓለም እርቆ ወደገዳም መሄዱ አዳም ከዚህ ዓለም እርቃ በምትገኘው ገነት ድልሆኖ ነበርና እርሱም ዲየብሎስን በገዳምና በዚህ
ዓለም እርቆ ድል አደረገልን ለኛም ፈቃደ ስጋችንን የምናሸንፍበትን ሃይል ሰጠን፡፡ይህ ጾም ጠላት ዲያብሎስ የተሸነፈበት ነው፡፡
5.
የመሸጋገሪያ ጾም ይባላል፡፡
ሊቀ ነቢያት ሙሴ ሕዝቡን ከህገ ልቦና ወደ ኦሪት ሲያሸጋግር አርባ መአልትና ለሊት
በደብረ ሲና እንደጾመው ጌታችንም እኛን ከህገ ኦሪት ወደ ህገ ወንጌል ሲያሸጋግረን አርባ መአልትና ለሊት ጸመ፡፡ስለዚህ
የመሸጋገርያ ጾም እንለዋለን፡፡
6.
ጾመ አስተምህሮ ይባላል ፡፡
ሁሉን ነገር በቅጽበትና ያለ ድካም ማድረግ የሚችለው አምላክ እኛን ልጆቹን
ያስተምረን ዘንድ እራሱን ዝቅ አደረገ፡፡መልካም መምህር ተማሪዎቹ ይገባቸው ዘንድ ዝቅ ብሎ በነርሱ ቋንቋ አየተናገረ በሚችሉት
እየመሰለ እንዲያስረዳ ጌታችንን እኛን ወደርሱ ይወስድ ዘንድ አስቀድሞ እርሱ ወደኛ መጣ፡፡ርሃባችንን ተራበ፣ድካማችንን
ደከመ፣ፈተናችንን ተፈተነ ለኛም አርአያ ሆኖ ትህትናን፣ትዕግስትንና ፈተናን በጾም አሸነፎ አስተማረን፡፡
7.
የቀድሶተ ገዳም ጾም ይባላል፡፡
እነ መጥምቁ ዩሐንስ አነ ነብዩ ኤሊያስ የኖሩትን የብሕትውና ኑሮ ጌታ ባርኮ ሰጠን
፡፡ከከተማ ወጥቶ ከሰው ርቆ በበረሃ ከአራዊት ጋር እየኖረ በዲያብሎስ ተፈትኖ ድል አደረግ ፡፡ዛሬም ልጆቹ በየገዳማቱ ድምጸ
አራዊትን ግርማ ሌሊትን ታግሰው ዓለምን ንቀው ፤ከሰው ርቀው
በጾም በጸሎት ከአጋንንት ጋር ይታገላሉ ድልም ያደርጋሉ፡፡
8.
የመዘጋጃ ጾም ይባላል፡፡
ለእስራኤላውያን ስለ በዓለ ፋሲካ አከባብር ሲነገራቸው የፋሲካውን በግ ሥጋ ከመራራ
ቅጠል ጋር እንዲበሉት ታዘው ነበር(ዘጸ12፤18)፡፡ይኸውም መራራ ቅጠል በግብጽ ይኖሩት የነበረውን የመከራ ኑሮ የሚያሳስባቸውና
ዳግም ወደ ገብጽ (ምድረ ፋይድ) እንዳይመለሱ ከኃጢያታቸው ይርቁ ዘንድ የሚያስተምራቸው ነበር፡፡የፋሲካ በግ ደግሞ እግዚአብሔር
በፍቅሩ የሰጣቸውን ነጻነት ያሳስባቸዋል
ዛሬም በኦርቶዶክሳዊት ተዋህዶ በቤተክርስቲያን ከበዓለ ትንሳኤው በፊት የጾም ወራት
ያስቀደምነው ለዚህ ነው፡፡ ከመብል ስንከለከል አዳምና ሔዋን የተሰጠውን ህግ እናስባለን እርሀብ ሲሰማን በሰው ልጅ ላይ ደርሶ
የነበረውን የጸጋ ርሃብና የመንፈስ ረሃብ ይታወስናል ስንደክም ስንጎሰቁል በአዳምን ሔዋን የደረሰው የመንፈስ ጉስቁልናና
የበደልን የእዳ ቀንበር ተሸክመው የደረሰባቸው ድካም ይታሰበናል፡፡እኛም በነርሱ የደረሰችው ሞት በእኛ እንዳትደርስ ዳግም ወደ
ኃጢያት እንዳንመለስ ይመክረናል፡፡
በጾሙም መጨረሻ የሐዲስ ኪዳንን በግ የጌታችን የመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን
ስጋና ደም እንቀበላለን ያን ጊዜም ሞትን ካሸነፈው አምላክ ጋር አንድ እንሆናለን ፡፡ሞታችን በሞቱ እንዳለፈ
እናስባለን(1ቆር11፤26)፡፡በመሆኑም ይህ ወቅት በዓለ ትንሳኤ የሐዲስ ኪዳን ፋሲካን ለማክበርና ሥጋወ ደሙን ለመቀበል
እራሳችንን የምናዘጋጅበት የምንፈትንበት ነው(1ቆር11፤27)፡፡
9.
የስራ መጀመሪያጾም ይባላል፡፡
ጌታችን መዳኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የማስተማር ስራውን ከመጀመሩ በፊት የመንግስት
ሰማያትን አንቀጽ ከማስተማሩ በፊት በገዳመ ቆሮንጦስ አርባ መአልትና ለሊት ጾመ፡፡ይህምም ለእኛ የማንኛውም ነገር መጀሪያው ጾም
መሆኑን ሲያስተምረን ነው፡፡ለዚህም ነው ሐዋርያት ጾምን የስራቸው መጀመሪያ ያደረጉት
እንግዲህ ዐብይ ጾም ማለት፡-
ጌታ ስለኛ ባየው መከራ የምናዝንበት፣
በሰጠን ኃይል ከሰይጣንና ከፈቃደ ስጋ የምንዋጋበት፣
በበደልነው ገብቶ የካሰልንን እያሰብን ዳግም ወደ ኃጢያት ላንመለስ ቃል
የምንገባበት፤አርአያ ሆኖ ከሠራልን ሥርዓት፤ከኖረልን ሕይወት የምንማርበት፤ራሳችንን ለፋሲካው በግ ለሥጋ ወደሙ የምናዘጋጅበት
ሰሞን ነው፡፡
በመሆኑም በሰላም፣በፍቅር፣በትህትና ጾመን ለበዓለ ትንሳኤው በሰላም እንድንደርስ
ጾመን ለማክበር እንዲያበቃን እግዚአብሔር በቸርነቱ ይጠብቀን አሜን!!!

ምንም አስተያየቶች የሉም:
አስተያየት ይለጥፉ